ከአዲግራት እስከ ዛላንበሳ፤ ቁርጥራጭ ማስታወሻዎች (ክፍል አንድ)
‘ለአዲሳባ “ሸገር” የሚል የዳቦ ስም ከሰጠን ለአዲግራት ምን እንላለን?’ የሚል የሚኒስትሪ ፈተና ጥያቄ ቢመጣ ስንት ተማሪ እንደሚመልሰው አላውቅም። “ወልዋሎ” ካሉ መልሱን አግኝተውታል፡፡ ይህ ስም በከተማዋ ሁሉም ነገር ላይ ተፅፎ ይታያል፡፡ “ወልዋሎ ፀጉር ቤት”፣”ወልዋሎ እንዳ-ባኒ” (ዳቦ ቤት ማለት ነው)፣ “ወልዋሎ ሙዚቃ ቤት”፣ “ወልዋሎ ጥህሎ ቤት”… “ወልዋሎ ከረንቡላ”…የወልዋሎ ነገር ማቆምያ የለውም፡፡ ከ ወልዋሎ የተረፉት አገልግሎት መስጫዎች ደግሞ “አግኣዚ” በሚል ነው የሚጠሩት፡፡ “አግአዚ” በአዲግራት ከተማ ከትምህርት ቤት እስከ ቡና ቤት ያለ ማንኛውም ድርጅት ሊጠራበት የሚችል ስም ነው፡፡ አግአዚ ቡቲክ፣አግአዚ ኢንተርኔት፣ አግኣዚ ትምህርት ቤት፣አግአዚ መሸታ ቤት…ወዘተ
በከተማዋ የሚገኘው ቁጥር አንድ የምሽት ክለብ “ፍሪ -ዞን” ይባላል፡፡ ለመዲናችን አዲስ አበባ እንኳ የሚመጥን ዘመናዊ ክለብ ነበር፡፡ ሆኖም ክለቡ ከከተማዋ በብዙ እርምጃ በመቅደሙ በገበያ እጦት ተዘግቷል፡፡ የዛሬን አያድርገውና አዲግራት የሞቀች-ያበደች፣ አሸሼ ገዳሜ የሚባልባት ከተማ ነበረች አሉ፡፡ የድንበር ጦርነት ጉሮሮዋን ዘጋው፡፡ ብዙዎቹ ነዋሪዎቿም ተሰደዱ፣ ወደ መቀሌ፣ወደ አዲሳባ፡፡

16 February 2011 